የኤሌክትሪክ መኪናን በ9 ደቂቃ ብቻ ሙሉ በሙሉ ቻርጅ የሚያደርግ ቴክኖሎጂ ይፋ ሆነ
በአውቶሞቢል ኢንዱስትሪ ውስጥ ግዙፍ ስም ያለው የቻይናው ቢ.ዋይ.ዲ (BYD) ኩባንያ፣ የኤሌክትሪክ መኪና ተጠቃሚዎችን ትልቁን ስጋት የሚቀርፍ እጅግ ፈጣን የቻርጅ ሲስተም ይፋ አደረገ።
ይህ አዲስ ቴክኖሎጂ የኤሌክትሪክ መኪናን ቻርጅ ለማድረግ የሚወስደውን ጊዜ ከነዳጅ መቅጃ ፍጥነት ጋር በማመጣጠን ረገድ አዲስ ምዕራፍ ከፋች ተብሏል።
እንደ ኩባንያው ገለጻ፣ አዲሱ ሲስተም እስከ 1,500 ኪሎ ዋት (1.5 Megawatt) የሚደርስ ከፍተኛ ኃይል የማመንጨት አቅም አለው። ይህም በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ ካሉ ፈጣን ቻርጀሮች በሦስት እጥፍ የሚበልጥ ፍጥነት እንዲኖረው አድርጎታል።
ይህ ቴክኖሎጂ ቢ.ዋይ.ዲ በቅርቡ ካመረተውና "ብሌድ ባትሪ" (Blade Battery) ከተሰኘው ዘመናዊ የባትሪ ቴክኖሎጂ ጋር ተቀናጅቶ የሚሰራ ሲሆን፣ አንድን መኪና ከጥቂት ደቂቃዎች ባነሰ ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ ቻርጅ ማድረግ ይችላል። በተለይም የኤሌክትሪክ ባትሪዎች ብቃት በሚቀንስበት በከፍተኛ ቅዝቃዜ ወቅት እንኳን ቴክኖሎጂው ያለምንም ችግር ፈጣን አገልግሎት እንዲሰጥ ተደርጎ ተቀርጿል።
የኤሌክትሪክ መኪና ተጠቃሚዎች በተለይም ረጅም መንገድ በሚጓዙበት ወቅት ቻርጅ ለማድረግ የሚወስድባቸው ረጅም ጊዜ፣ ብዙዎች ከነዳጅ መኪና ወደ ኤሌክትሪክ እንዳይቀይሩ እንደ ትልቅ እንቅፋት ሲጠቀስ ቆይቷል።
ይህ አዲስ ፈጠራ ግን "ቻርጅ ለማድረግ ይቆያል" የሚለውን ስጋት (Range Anxiety) ሙሉ በሙሉ እንደሚያስቀረው ታምኖበታል።
ቢ.ዋይ.ዲ ይህንን እጅግ ፈጣን ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያዎች በቻይና ዋና ዋና አውራ ጎዳናዎችና ከተሞች ውስጥ በሺዎች የሚቆጠሩ ለመገንባት ማቀዱን አስታውቋል።
ይህ እርምጃ ዓለም አቀፉን የትራንስፖርት ዘርፍ ወደ ንጹህ ኢነርጂ ለማሸጋገር የሚደረገውን ጥረት በእጅጉ እንደሚያፋጥነው የዘርፉ ተንታኞች ገልጸዋል።
#afromekina
Loading content...
